Home > News > ሃገር ቤት ባለው ሲኖዶስ የሃሳብ ልዩነት ተፈጠረ

ሃገር ቤት ባለው ሲኖዶስ የሃሳብ ልዩነት ተፈጠረ

December 21, 2012

መንግስት ፓትርያርክ ሊያደርጋቸው ካቀረባቸው እጩዎች መካከል አሜሪካዊ ዜግነት ያላቸው ብጹእ አቡነ ማትያስ።

(ዘ-ሐበሻ) ትናንት በሰበር ዜና “ኢትዮጵያ ያለው ሲኖዶስ ፓትርያርክ ለመምረጥ አስመራጭ ጳጳትን መረጠ” የሚል ዜና ማስነበባችን ይታወሳል። የሲኖዶሱ ስብሰባ ሳይጠናቀቅ የተወሰኑ አባቶች በተለይ ውጭ ያለው ሲኖዶስ ጋር የሚደረገው እርቀ ሰላም ሳይጠናቀቅ ፓትርያርክ እንዳይመረጥ በመቃወም ስብሰባውን ረግጠው መውጣታቸውንና አንዳንድ አባቶችም በስብሰባው ላይ እንዳልተገኙ የዘ-ሐበሻ የቤተክህነት ታማኝ ምንጮች ጠቆሙ።

እነዚሁ ምንጮች ፓትርያርክ እንዲሾም በአስመራጭነት ከተመረጡት ከቅ/ሲኖዶስ አባላት፣ ከመ/ፓ/ጠ/ቤ/ክ መምሪያ ሓላፊዎች፣ ከገዳማት አበምኔቶች፣ ከሰንበት ት/ቤቶች አንድነት፣ ከመንፈሳውያን ማኅበራት እና ከታዋቂ ምእመናን የተውጣጡ ናቸው ከተባሉት 13 ሰዎች መካከል 8ቱ ከአንድ ብሄር የመጡ መሆናቸው የጉዳዩን ፖለቲካነት የበለጠ አጉልቶታል ያሉት ምንጮቹ ከነዚህ አስመራጮች መካከል ከአንድ ብሄር ከመጡት 8 ሰዎች ውስጥ አቡነ ጢሞጢዎስ፣ አቡነ እስጢፋኖስ፣ መጋቤ ምስጢር አምደብርሃን፣ ንቡረ ዕድ እዝራ እንደሚገኙበት አስታውቀዋል።

በተለይ አሜሪካ ከሚገኘው ሲኖዶስ ጋር እርቀ ሰላም ላይ የነበሩት አባቶች አቡነ ገሪማ፣ አቡነ አትናቲዎስ፣ አቡነ ቀውስጦስ በዚህ ፓትርያርክ አስመራጭ ኮሚቴ በተመረጠበት ስብሰባ ላይ እንዳልተገኙ የጠቆሙት እነዚሁ ምንጮቻችን አቡነ ኤልሳ እና በውጭ ሃገር ያሉ ጳጳሳት ሁሉ እንዳልተገኙና ድርጊቱን መቃወማቸውን እንዲሁም በአብዛኛው ፓትርያርክ እንዲሾም በመወትወት ላይ የሚገኙት ከመንግስት አስገዳጅነት ጋር ከአንድ ብሄር የመጡ አባቶች መሆናቸውን ገልጸዋል።

በተለይም አቡነ ሉቃስና አቡነ ቄርሎስ ይህን የሲኖዶሱን ስብሰባ ጥለው እንደወጡ ያስታወቁት ምንጮች በሲኖዶሱ ውስት በ6ኛው ፓትርያርክ ሹመት ዙሪያ የሃሳብ ልዩነት እንደተፈጠረ አስታውቀው እንደውም አቡነ አትናቲዎስ ድርጊቱን አምርረው መቃወማቸውንና ምርጫውን እንደማይቀበሉት በይፋ መናገራቸው ታውቋል።

በመንግስት ከፍተኛ ጫና 6ኛ ፓትርያርክ በአፋጣኝ ለመሾም የሚደረገው ጥረት በበርካታ የኦርቶዶክስ ተዋሕዶ እምነት ተከታዮች ዘንድ ተቃውሞ እየገጠመው ይገኛል። የሲኖዶሱ ስብሰባ ከተጠናቀቀ በኋላ የሲኖዶሱ ጸሐፊ አቡነ እዝቅኤል መግለጫ እንዲሰጡ ተጠይቀው ፈቃደኛ ባይሆኑም ስብሰባው የተጠናቀቀው በሃሳብ ልዩነት መሆኑን ምንጮቻችን ተናግረዋል።

Source: Zehabesha.com

Categories: News